Thursday, January 31, 2013

2013 Human Rights Watch Report (Ethiopia)

January 31, 2013 

የ 2013 የዓለም የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ሪፖርት፡- ኢትዮጵያ

ኢትዮጵያን ለረጅም ዓመታት በጠቅላይ ሚኒስትርነት የመሩትና ሰፊ ስልጣን የነበራቸው መለስ ዜናዊ በነሃሴ ወር በድንገት መሞት በሃገር ውስጥም ሆነ በኢትዮጵያ ዓለማቀፍ አጋሮች ዘንድ የሀገሪቱን ፖለቲካዊ ሽግግር የሚመለከቱ ጥያቄዎችንና አጠራጣሪ ሁኔታዎችን አስነስቶ ነበር።በኢትዮጵያ ያለው የሰብአዊ መብቶች አያያዝ በተለይ ካለፉት ጥቂት ዓመታት ወዲህ እየከፋ ሄዷል።አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በመስከረም ወር ስልጣኑን የተረከቡ ቢሆንም መንግስት በርሳቸው አመራር ሰብአዊ መብቶችን የሚመለከቱ ለውጦች ያደርግ ወይስ አያደርግ እንደሆነ ገና የሚታይ ነው።
እ.ኤ.አ በ2012ም የኢትዮጵያ ባለስልጣናት መሰረታዊ የሆኑትን ሃሳብን በነጻ የመግለጽ፣ የመደራጀት እና የመሰብሰብ መብቶች በጥብቅ መገደባቸውን ቀጥለዋል።ለኣሻሚ ትርጉሞች በተጋለጠውና በ2002 ዓ.ም በወጣው የሀገሪቱ የጸረ ሽብርተኝነት ሕግ 30 ጋዜጠኞችና የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ አባላት ተከሰው ተፈርዶባቸዋል።በዋና ከተማዪቱ አዲስ አበባ እና በኦሮሚያ ክልል የእስልምና እምነት ተከታዮች ላካሄዷቸው የተቃውሞ ሰልፎች የጸጥታ ሃይሎች የሰጡት ምላሽ የዘፈቀደ አፈሳ፣ እስር እና ድብደባ ነበር።
የኢትዮጵያ መንግስት በአምስት ክልሎች የሚኖሩ የገጠር ነዋሪዎችን የተሻለ የመሰረታዊ ግልጋሎቶች አቅርቦት ሊያገኙ ወደሚችሉባቸው አካባቢዎች ለመውሰድ በሚል ምክንያት 1.5 ሚሊዮን የገጠር ነዋሪዎችን መልሶ ለማስፈር የሚያካሂደውን የሰፈራ ፕሮግራም ቀጥሎበታል።በጋምቤላ ክልል የሚገኙ በርካታ ነዋሪዎች ከፍላጎታቸው ውጭ በሃይል እንዲፈናቀሉ በመደረጋቸው ለከፍተኛ ችግሮች ተጋልጠዋል። ከዚህ በተጨማሪም መንግስት ለሚያካሂደው ሰፊ የስኳር ልማት መሬት ለማስለቀቅ ሲባል በኢትዮጵያ የታችኛው ኦሞ ሸለቆ ነዋሪ የሆኑትን አርብቶ አደር ማህበረሰቦች ከመኖሪያቸው እንዲፈናቀሉ እያደረገ ነው።
ሃሳብን በነጻ የመግለጽ፣የመደራጀት እና የመሰብሰብ መብቶች

መንግስታዊ ያልሆኑ ደርጅቶችን እንቅስቃሴ ለመቆጣጠር  የበጎ አድራጎት ደርጅቶች እና ማህበራት አዋጅ እንዲሁም የጸረ ሽብርተኝነት ሕግ በ2002 ዓ.ም ከታወጁ ወዲህ በኢትዮጵያ ሃሳብን በነጻ የመግለጽ፣የመሰብሰብ እና የመደራጀት መብቶች ከፍተኛ ገደብ ተጥሎባቸዋል። እነዚህ ሁለት ሕጎች መንግስት በሲቪል ማህበረሰብ መሪዎች፣በጋዜጠኞች እና በሌሎችም የመንግስትን ፖሊሲ በሚተቹና መንግስት እንዲነሱ በማይፈልጋቸው ጉዳዮች ላይ ሃሳባቸውን በሚገልጹ ሰዎች ላይ ካካሄደው ሰፊ እና የማያቋርጥ ማዋከብ፣ዛቻ እና ማስፈራራት ጋር ተዳምሮ ያስከተሉት  ውጤት የከፋ ነው።
ኢትዮጵያ ውስጥ እጅግ የጎላ እንቅስቃሴ ያደርጉ የነበሩ የሰብአዊ መብቶች ድርጅቶች እንቅስቃሴዎቻቸውን በከፍተኛ ሁኔታ እንዲቀንሱ ወይም ሰብአዊ መብቶችን የሚመለከቱ ጉዳዮችን ከስራ ዝርዝራቸው ውስጥ እንዲያወጡ የተገደዱ ሲሆን ቁጥራቸው ያልታወቀ ድርጅቶችም ጭራሹኑ ተዘግተዋል። በደረሰባቸው ማስፈራሪያ ምክንያት ሰፊ ልምድና መልካም ስም የነበራቸው ብዙ የሰብአዊ መብቶች ተሟጋቾች ሃገሪቱን ለቀው ሄደዋል። አሁን ሰፍኖ የሚገኘው ሁኔታ ለነጻ ፕሬስ እንቅስቃሴም እንዲሁ የተመቸ አይደለም።ባለፉት አስር ዓመታት በደረሰባቸው ዛቻ እና ማስፈራራት ሳቢያ ሃገራቸውን ለመልቀቅ በተገደዱ ጋዜጠኞች ቁጥር በዓለም ኢትዮጵያ ቀዳሚዋ ናት። የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች የሆነው ድርጅት ሲፒጄ እንደሚገልጸው ቢያንስ 79 ጋዜጠኞች ሃገራቸውን ለቀው ለመሰደድ ተገደዋል።
የጸረ ሽብርተኝነት አዋጁ፣ ተቃዋሚ ናቸው ተብለው የሚታሰቡ ሰዎችን ዒላማ ለማድረግ፣ተቃውሞን ለማፈን እና ጋዜጠኞችን ዝም ለማሰኘት ስራ ላይ እየዋለ ነው። እ.ኤ.አ በ2012 ዓ.ም 30 የፖለቲካ መሪዎች፣ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት እንዲሁም ጋዜጠኞች በግልጽ ባልተብራሩ የሽብርተኝነት ወንጀሎች ተከሰው ተፈርዶባቸዋል።ከ2011 ጀምሮ ባለው ጊዜ ውስጥ 11 ጋዜጠኞች በዚሁ ሕግ ተከሰው ተፈርዶባቸዋል።

ጥር 17 ቀን 2004 ዓ.ም አሁን የተዘጋው አውራምባ ታይምስ ጋዜጣ ምክትል አዘጋጅ በነበረው ውብሸት ታዬ እና የጋዜጣው ዓምደኛ በነበረችው ርዕዮት ዓለሙ ላይ በአዲስ አበባ የሚገኝ ፍርድ ቤት የ 14 ዓመታት እስር ፈርዶባቸዋል።የርዕዮት ዓለሙ ፍርድ በኋላ በይግባኝ ወደ አምስት ዓመታት የተቀነሰ ሲሆን ከቀረቡባት ክሶች ውስጥም አብዛኞቹ ተሰርዘዋል።
ከፍተኛ ክብር ያለውን የፔን አሜሪካ ፍሪደም ቱ ራይት ሽልማት በሚያዝያ ወር 2004 ዓ.ም ያሸነፈው አንጋፋው ጋዜጠኛ እና ብሎገር እስክንድር ነጋ ሐምሌ 6 ቀን 2004 ዓ.ም ከሌሎች ጋዜጠኞችና የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ጋር በቀረበበት ክስ የ 18 ዓመታት እስራት ተፈርዶበታል። በስደት ላይ የሚገኙት ጋዜጠኞች አብይ ተክለማርያም እና መስፍን ነጋሽም እስካሁን ድረስ ጋዜጠኞች ላይ ብቻ ተግባራዊ በተደረገው የጸረ ሽብርተኝነት ሕጉ አንቀጽ መሰረት ጥፋተኛ ተብለው እያንዳንዳቸው የ 8 ዓመታት እስራት ተፈርዶባቸዋል። በይፋ ተመዝግቦ የሚንቀሳቀሰው ተቃዋሚ ፓርቲ አንድነት ለፍትሕ እና ለዲሞክራሲ አባል የሆነው አንዷለም አራጌ በስለላ፣ሕገ መንግስታዊ ስርዓቱን በመናድ እንዲሁም የሽብር ተግባር ለመፈጸም ምልመላ እና ስልጠና በማካሄድ ወንጀሎች ጥፋተኛ ተብሎ የዕድሜ ልክ እስራት ተፈርዶበታል።
በመስከረም ወር 2004 ዓ.ም የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የእስክንድር ነጋ እና በስደት ላይ የሚገኘው ጋዜጠኛ አበበ በለው  እንዲሁም የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ አባሉ አንዷለም አራጌ ንብረቶች እንዲወረሱ ትዕዛዝ ሰጥቷል።
 
 click the link for full reporthttp://www.hrw.org/world-report/2013/country-chapters/112447