Monday, June 9, 2014







በአንድነት እና በመኢአድ መካከል የተደረገው ውህደት በተመለከተ የተሰጠ መግለጫ – የሰሜን አሜሪካ የአንድነት የድጋፍ ማህበራት

 ሰኔ ፪ 2006
ተሰናክለን ነበር፤ አሁን ግን ጸንተናል!

«ዉጊያዉን ተሸነፍን እንጂ ጦርነቱን አልተሸነፍንም» ነበር ያሉት የፈረንሳዩ የ2ኛው ዓለም ጦርነት መሪ፤ ጀነራል ቻርለስ ደጎል፣ አገራቸው በናዚዎች ሥር በወደቀች ጊዜ። ልክ እንደ ዉትድርናዉም፣ በሰላማዊ ትግል ዉስጥ መሸነፍ፣ መዉደቅ፣ መሳሳት አለ። መነሳትም እንዲሁ፡፡ ታላቁ የነጻነት ታጋይ ኔልሰን ማንዴላ እንዳሉትም፤ «በሕይወት ውስጥ ትልቁ ነገር ፈጽሞ አለመውደቅ ሳይሆን፤ በወደቁ ቁጥር መነሳት ነው»
በአገራችን የሰፈነዉን አምባገነንነት በመቃወምና በአገራችን ሰላም፣ ዴሞክራሲ፣ የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን፣ ላለፉት አያሌ አመታት ትእግስት አስጨራሽ ትግል ቢደረግም፤ የተደረጉ ጥረቶች የተፈለገውን ዉጤት ሳያመጡ ቀርተዋል፡፡
በተለይ በምርጫ ዘጣና ሰባት ወቅት፣ በአገር ዉስጥና ከአገር ዉጭ ያለውን ኢትዮጵያዊ ሁሉ የሚያነቋንቅ ትልቅ ሥራ ተሰርቶ የነበረ ቢሆንም፣ ቅንጅትን በመሰረቱ ድርጅቶች መካከል ልዩነቶች ስለተፈጠሩ፣ የቅንጅት አመራር አባላትም በተለያዩ ምክንያቶች ስለተከፋፈሉ፣ የአገዛዙ አፈናና የረቀቀ ከፋፋይ ሴራ ተጨምሮበት፣ ያኔ የነበረዉ የቅንጅት አብዮት እንዲቀዘቅዝ ሆኗል፡፡። ይህም የአምባገነኖች ደስታ ሆኖ ቆይቷል።
ነገር ግን ደጎል እንዳሉት፤ ለግዜው ተሰናክለን ወደቅን እንጂ ተስፋ አልቆረጥንም። ተነሳን እንጂ፤ ወድቀን አልቀረንም፡፡ ላለፉት ሶስት አራት አመታት የመቀራረብና አብሮ የመስራት መንፈስ በተቃዋሚዎች መካከል ሥር እየሰደደ ሲመጣ ታዝበናል። አገር ቤት አሉ ከሚባሉ ጠንካራ ደርጅት መካከል፣ የአንድነት ፓርቲ፣ ከብርሃን ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ጋር ከሶስት አመታት በፊት ውህደት የፈጠረ ሲሆን፣ አንድነት ከሌላው አንጋፋ ድርጅት መኢአድ ጋር ለመዋሃድ ንግግሮችን ሲያደርግ ቆይቷል።
ሲደረጉ የነበሩ አድካሚ ንግግሮች ፍሬ አፍርተዉ፣ በመኢአድና በአንድነት መካከል የቅድመ ዉህደት ስምምነት ሰኔ አንድ 2006 ዓ.ም ተፈርሟል። ይህ ታሪካዊ ክስተት ለድርጅታችንም ሆነ ለመላዉ ነጻነት ናፋቂ የኢትዮጵያ ህዝብ ትልቅ ደስታና ተስፋ ፈንጣቂ ነው ብለን እናምናለን። የመኢአድና የአንድነት አመራር አባላትን ድርድራቸው ለዚህ በመብቃቱ እንኳን ደስ አላችሁ እያልን፤ ይህን አይነት መልካም ዜና ስላሰሙንም ልናመሰግናቸው እንወዳለን። ውህደቱም ሙሉ ለሙሉ እንደሚሳካ ተስፋ እናደርጋለን፡፡
ማህበራችን በምኞትና በቃላት ብቻ ሳይሆን በተግባር፣ የዚህ ታሪካዊ፣ ወሳኝ ትግል አጋር በመሆን የድርሻዉን እንደሚወጣ በዚህ አጋጧሚ ቃል እንገባለን።
ሌሎችም በሰላማዊ ትግል አገር ቤት የሚንቀሳቀሱ ድርጅቶችም ፣ መኢአድ እና አንድነትን እንዲቀላቀሉ ጥሪ እያቀረብን፣ በዉጭ ያሉ በሰላማዊ ትግል የሚያምኑ ደርጅቶችም ለአገርና ለሕዝብ ጥቅም ሲሉ ይህን ውህደት እዲደግፉና እንዲሰባሰቡ ጥሪ እናቀርባለን።
አንድነትና/መኢአድ ትግሉን በስሜት ሳይሆን በማስተዋል፣ በችኮላ ሳይሆን በእርጋታ፣ በጥላቻ ሳይሆን በፍቅር፥ በማራቅ ሳይሆን በማቅረብ እንዲመሩት እንመክራለን። ስህተቶች ይሰራሉ፤ ነገር ግን በስህተቶች የመደናገጥና በቀላሉ ተስፋ የመቆረጥ ዝንባሌያችን አስተካክለን፣ ለፈታኝ እና ወሳኝ ትግል ሁላችንም እንዘጋጅ። ሁላችንም የድርሻችንን ለመወጣት እንነሳ።
በአጭር ግዜ የድርጅቱ ሙሉ ውህደት ተጠናቆ፤ ውህድ ድርጅቱ ለመጪው ምርጫም ይሁን ቀጣይ ትግል የሚያዘጋጁ የፖሊሲ ውይቶችን እንደሚጀምር፤ የበሰለ አመራር በመስጠት እንደ 1997ቱ ሁሉ ጠንካራ ተፎካካሪ ሆኖ እንደሚወጣ እንጠብቃለን፡፡
በሰሜን አሜሪካ የምንገኝ የድጋፍ ማህበራት፤ በሁለቱ ድርጅቶች ደጋፊዎች መካከል ውህደት እንዲኖር እንደምንተጋ፤ እንዲሁም ውህድ ድርጅቱን በገንዘብ፤ በቁሳቁስ፤ በሞራልና በዲፕሎማሲ እንደምንረዳ ቃል እንገባለን፡፡
ነጻነት የትግል ውጤት ነው!!
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!!udJAEUP