Sunday, September 8, 2013

Thursday, September 5, 2013

   “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” የ3ወር መርሃ-ግብር በታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ይጠናቀቃል!

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)
UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)
 “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” የ3ወር መርሃ-ግብር በታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ይጠናቀቃል!
 በአንድነትና በ33ቱ ፓርቲዎች በጋራ የተሠጠ ጋዜጣዊ መግለጫ
                                                አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ(አንድነት) ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል እንቅስቃሴ የበለጠ ተጠናክሮ ህዝቡ የትግሉ መሪ ተዋናይና ባለቤትነት እንዲረጋገጥ ላለፉት ሶስት ወራት ፓርቲያችን ባስቀመጠው ስትራቴጂ እቅድ መሠረት ሰፊ ህዝባዊ ንቅናቄ ሲያደርግ ቆይቱዋል፡፡
በሃገራችን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ማለትም ፖለቲካዊ፤ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንዲሁም የዜጎች ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች መረገጥ ፓርቲያችን “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” በሚል ሰኔ 13ቀን 2005 በይፋ ለጀመረው ሕዝባዊ ንቅናቄ ፖለቲካዊ ምክንያቶች ናቸው፡፡
ሕዝባዊ ንቅናቄው በእቅድ መመራት ከመጀመሩ በፊት ሀገራችን የምትገኝበትን ነባራዊ ሁኔታና የህዝባችን ተጨባጭ ኑሮ ላይ ጥናት በማድረግ የመፍትሄ አማራጮችን ማቅረቡ የፓርቲያችን አብይ ጥያቄ ሆኖ መገኘቱም የንቅናቄውን ወቅታዊነት ያገናዘበ አድርጎታል፡፡
በእቅዳችን መሰረት በመላው ሃገሪቱ ለመጀመሪያው ዙር በተመረጡ ቦታዎች ያደረግናቸው ህዝባዊ ስብሰባዎችና ሰላማዊ ሰልፎች በአባሎቻችን፤ በደጋፊዎቻችንና በህዝባችን ጠንካራ ትግልና መስዋእትነት ንቅናቄው የተሳካ ሲሆን ፓርቲያችን ለተከፈለው ዋጋ ሁሉ አድናቆቱን ይገልፃል፡፡
በገዢው ፓርቲ ካድሬዎች በመታገዝ የፀጥታ ኃይሎች እንቅስቃሴዎቻችንን ለማጨናገፍ ከህግና ሥርዓት ውጪ ማስፈራራት፤ ማሸማቀቅ፤እስራትና ድብደባ በአባሎቻችን ላይ ሰብአዊነት በጎደለው ሁኔታ ተፈፅሞባቸዋል፡፡ የቅስቀሳ ቁሳቁስም በአካባቢ የፀጥታ ሰራተኞች ተዘርፈውብናል፡፡ እንዲሁም ህዝብ በነፃ አስተሳሰብ አማራጩን እንዳይከተል በአካባቢ ካድሬዎችና አመራሮች ማስፈራራትና ዛቻ ደርሶበታል፡፡ መርሃ ግብሩም ከተፈፀመ በኃላም ቢሆን ህዝባዊ ንቅናቄውን የተቀላቀሉ ዜጎቻችን በመኖሪያ ቀያቸው ሰርቶ የማደርና በነፃነት የመኖር መብታቸው አደጋ ላይ ነው፡፡
በተንቀሳቀስንባቸው አካባቢዎች ሁሉ ገዢው ፓርቲ ከህዝብ የተነጠለ መሆኑንና ህዝቡን እየመራሁ ነው የሚለው ህዘብን በማሸማቀቅ እንደሆነ መገንዘብ ችለናል፡፡ ከህግ ውጭ የገጠሙን መንግስታዊ ተፅእኖዎች ሁሉ ነፃነቱን በተነፈገውና በለውጥ ፈላጊው ህዘባችን ህዝባዊ እምቢተኝነት ተልኮአችን ሊሳካ ችልዋል፡፡
የሚሊዮኖችን ድምፅ ለማሰባሰብ እየተደረገ ያለው እንቅስቃሴም በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር ያሉ ዜጎቻችን በንቃትና በቁጭት የተሳተፍበት በመሆኑ አመርቂ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ፊርማ የማሰባሰቡ መርሃ ግብር የሚቀጥል ይሆናል፡፡
የህዝባዊ ንቅናቄው የመጀመሪያው ዙር መርሃ ግብር በመዲናችን አዲስ አበባ ከተማ መስከረም 5ቀን 2006 በሚደረገው ታላቅ ህዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ይህ ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ እስካሁን ካደረግናቸው ህዝባዊ ንቅናቄዎች ልዩ የሚያደርገው የ33ቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ይሁንታ ያገኘና ሰላማዊ ሰልፉን በባለድርሻነት የተሳተፉበት መሆኑ ነው፡፡
በአንፃሩ ገዢው ፓርቲ እስካሁን ካወጣቸው አፋኝ ህጎች በተጨማሪ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ተጠናክሮ የመጣውን ህዝባዊ የፖለቲካ ተቃውሞ የበለጠ ለመደፍጠጥ አሳሪ ደንቦች ለማውጣት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እየተንቀሳቀሰ ለመሆኑ ከገጠመን መልካም አስተዳደር እጦት መገንዘብ ችለናል፡፡
የአንድነት ፓርቲና የ33ቱ ፓርቲዎች በጋራ በጠሩት በዚህ ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ህዝቡ በነቂስ ወጥቶ የነፃነት ድምፁን እንዲያሰማ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡
                                                     “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት”