Sunday, May 8, 2011

ቶሮንቶ በበቃ ተጠመቀች፤ ከተለያዩ ማህበረሰብ የተወጣጡ ኢትዮጵያዊያን የተሳካ ስብሰባ አካሄዱ

በተክለሚካኤል አበበ
ቅዳሜ ሜይ 7 ቀን በካናዳ የንግድ ከተማ፡ ቶሮንቶ ከተለያዩ ማህበረሰብ የተወጣጡ ኢትዮጵያዊያን ተናጋሪዎችና ተሳታፊዎች የነበሩበት የተሳካ የበቃ ንቅናቄ ስብሰባ ተካሄደ። ተጋባዥ እንግዶቹም አብሮ የመስራትና የጋራ ዓላማን የሚያሳይ የአቋም መግለጫ አወጡ። በዚህ ስብሰባ ላይ በመቶዎች የሚቆጠሩ የኦጋዴን የአፋርና የኦሮሞ ብሄረሰብ አባላትና ሌሎች ኢትዮጵያዊያንም የተገኙ ሲሆን፡ በመጨረሻም፡ ኢትዮጵያ አንድ ነች፡ አንድነታችን ግን በተለያዩ ማህበረሰቦች የተገነባ አንድነት ነው፡ እንዲሁም በዚህች ኢትዮጵያ ውስጥ የሰውነት የተፈጥሮ መብታችንን አስቀድሞ ማስከበር ከምንም በላይ ቅድሚያ የሚሰጠው ነገር ነው ሲሉ የአቋም መግለጫ አውጥተዋል።

በስብሰባው የመጀመሪያው ተናጋሪ የነበሩት፡ ከታላቁ የአፋር ብሄረሰብ የወጡት አቶ አሎ አይደሂስ፡ ሕወሀት/ኢህአዴግ በማሳ ውስጥ እንደበቀልና፡ እህሎቹን እንደሚያቀጭጭ አንድ አላስፈላጊ ዛፍ ነው ሲሉ መስለውት፡ አንድ ላይ አይቀመጡም፡ አይወያዩም፡ ብሎ ያስቀመጠን ተቃዋሚዎች ዛሬ ግን ባንድ ላይ መሰብሰባችን እጅግ እንዳስደሰታቸውና ወደፊትም መቀጠል እንዳለባቸው ተናግረዋል። በመጨረሻም ይህ ዛፍ መርዘኛ ስለሆነና እህሎቹን ስላቀጨጫቸው ከስሩ ለመነቀልና በአገራችን ፍትህና ርትእ ለማስፈን አብረን መስራት እንዳለብን አሳስበው ንግራቸውን ደምድመዋል።
ሁለተኛው ተናጋሪ ከኦጋዴን ማህበረሰብ የወጡት አቶ መሀመድ ሀሰን፡ እድሜ ልካችንን በማይረቡ ነገሮች ስንጨቃጨቅ ከምንኖር ይልቅ፡ የቋንቋ አንድነት፡ የሀይማኖት አንድነት፡ የአስተሳሰብ አንድነት፡ ሰይሆን የ“የምክንያት ወይንም የአላማ አንድነት (Unity of Purpose)” አንድነት ፈጥረን፡ አገራችንን እያጠፋ ያለውን ስርአት ማስወገድ አለብን ብለዋል። ሕወሀት/ኢህአዴግ ላለፉት አመታት በተለይም በኦጋዴን አካባቢ ከፍተኛ የሆነ እልቂት ሲፈጽም ገና ለገና ተገንጣይ ቡድኖች ናቸው ብሎ በማሰብና በመፍራት፡ በውጭ የምንገኝ ኢትዮጵያዊያን በሙሉ በኦጋዴን የተፈጸመውን የዘር ማጥፋት ወንጀል ተቃውመን በአንድነት አለመውጣታችን እጅግ እንደጎዳን ገልጸው፡ አሁንም ወያኔ ለምእራባዊያን የሚሸጠውን የፈጠራ ፖለቲካ ተባብረን ካልደመሰስነው በስተቀር፡ ርስ በርሳችን ስንባላ ያቺ የምንወዳት አገር ልትጠፋ እንደምንችል አሳስቦ፡ የጋራ ዓላማ ይዘን እንድንንቀሳቀስ አሳስቧል።
ሶስተኛ ተናጋሪ የሆነው አቶ አበበ በለውም፡ አሁን የስራ ጊዜ ነው፡ ጠላቶቻችን እያንዳንዱን ሰዓት አፈናም ይሁን ዝርፊያ በስራ ያሳልፉታል፡ እኛ ግን እስካሁን ከወሬ ደረጃ እንዳላለፍን ገልጾ፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ያንዱ ብሄር ችግር የዚያ ብሄር ብቻ ሳይሆን የሁሉም ኢትዮጵያዊ እንደሆነ በማሳሰብ የአብሮ መስራትን አስፈላጊነት ገልጿል።
አራተኛው ተናጋሪ ወጣት ጃዋር መሀመድ ሲሆን፡ ወጣት ጃዋር፡ በኢትዮጵያ ውስጥ ዴሞክራሲን በማስፈን፡ የመፈረካከስ አደጋን ለማቆም ህዝቡና ተቃዋሚ ፖለቲከኞች ማድረግ ስለሚገባቸው ነገሮች ተናግሯል። ጃዋር፡ አሁን ባለው ሁኔታ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች ህዝቡን ቀድመው መሄድና ማስተባበር ካልቻሉ፡ ህዝቡ ራሱ ቀድሞ በመተባበርና አብሮ በመስራት፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የፍትህና ስርአት ለውጥ እንዲመጣ፡ እንዲተጋ አሳስቧል። አሁን ባለው ሁኔታ ፖለቲከኞች ደጋፊ እናጣለን በሚል ፍራቻ የተነሳ ተፈራርተውና ተራርቀው እንደሚገኙ ገልጾ፡ ነገር ግን በመተማመንና በመተባበር ለመስራት፡ የአንድነትም ይሁን የነጻነት አራማጆች፡ ጽንፈኛነታቸውን ትተው ወደመሀል በመምጣት ነገሮችን አስታርቀው የመሄድ ባህል እንዲያዳብሩ ግድ እንደሚል ተናግሯል።
በመጨረሻም አቶ ኦባንግ ከራሱም ልምድና ከአገራችን ወቅታዊ ሁኔታ አንጻር ሰፊ ማብራሪያ አሰምቶ፡ ሁላችንም ነጻ ካልወጣን አንዳችንም ነጻ እንደማንወጣ፡ ከብሄራችንም በፊት ሰውነታችን መቅደም እንዳበት አሳስቦ የአብሮ መስራትን አስፈላጊነት አበክሮ ገልጿል። አቶ ኦባንግ ጠላታችን ይሄ ብሄር ወይንማ ያኛው ብሄር ሳይሆን፡ ስርአት እንደሆነ ገልጾ፡ ያንን ስርአት ለመጣል እንድንታገል አደራ ብሏል።
በመጨረሻም “አንድነት ሀይል ነው” በሚል መፈክር የተጀመረው ስብሰባ፡ አምስቱም ተናጋሪዎች በጋራ ባወጡት “አንድነት ሀይል ነው” እንዲሁም መለያየት በቃ መግለጫ ተጠናቋል። በዚህ ስብሰባ ላይ ከታየው የህዝብ ስብጥር በተጨማሪ፡ የስብሰባው አስተባባሪና የመድረክ መሪ አወያይዋ፡ ወይዘሮ ፋሲካ ወልደሰንበት አስደናቂና አስደሳች የአወያይ ሚና ተጫውታለች። ተመሳሳይ ስብሰባና የበቃ እንቅስቃሴ በሚቀጥለው ሳምንትም የሚቀጥል ሲሆን፡ ዶ/ር ወንድሙ መኮንን፡ ዶ/ር ቡሻ ታአና አቶ መስፍን ተፈራ ንግግር በቶሮንቶ እንደሚያደርጉ ታውቋል።
 

No comments: